settings icon
share icon
ጥያቄ፤

የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ጥቅሙ ምንድነው?

መልስ፤


የኢየሱስ ትንሣኤ በብዙ ምክንያቶች ጠቃሚ ነው። በቅድሚያ፣ ትንሣኤ ስለ እግዚአብሔር ስለ ራሱ ብርቱ ኃይል ምስክር ነው። በትንሣኤ ማመን በእግዚአብሔር ማመን ነው። እግዚአብሔር ሕያው ከሆነ፣ እናም እሱ ዩኒቨርስን ከፈጠረና በእርሱ ላይ ሥልጣን ካለው፣ እንግዲያውስ ሙታንን ለማስነሣት ሥልጣን አለው ማለት ነው። እሱ ይህን የመሰለ ሥልጣን ከሌለው፣ እሱ የእኛ እምነትና አምልኮ የሚገባው አይሆንም። ሕይወትን የፈጠረ ብቻ ነው፣ ከሞት በኋላ ሊያስነሣው የሚችል፣ አስፈሪውን ሞትን ራሱን መገልበጥ የሚችለው እሱ ብቻ ነው፣ እንዲሁም ውጉን መንቀል የሚችለውና፣ በመቃብር ላይ ድልን መቀዳጀት የሚችለው እሱ ብቻ ነው (1 ቆሮንቶስ 15፡54-55)። ኢየሱስን ከመቃብር በማስነሣት፣ እግዚአብሔር ፍጹም የሆነ ሉዓላዊነቱን በሕይወትና በሞት ላይ አስታውሶናል።

የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ደግሞ ጠቃሚ ነው፣ ምክንያቱም ኢየሱስ ማንነቱን የሚያስረግጠውን እውን ስለሚያደርገው ነው፣ በስያሜውም የእግዚአብሔር ልጅ እና መሲሕ። እንደ ኢየሱስ፣ የእርሱ ትንሣኤ “ከሰማይ የሆነ ምልክት” ነው፣ አገልግሎቱን አረጋግጧል/አጽንቷል (ማቴዎስ 16፡1-4)። የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በመቶዎች የዓይን ምስክሮች ተረጋግጧል (1 ቆሮንቶስ 15፡3-8)፣ ይህም ሊካድ የማይቻል ማስረጃ ይሰጠናል፣ እሱ የዓለም አዳኝ ለመሆኑ።

የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ጠቃሚ ለመሆኑ ሌላኛው ምክንያት፣ የእርሱን ኃጢአት-የለሽ ባሕርይና መለኮታዊ ማንነቱን ስለሚያረጋግጥ ነው። ቅዱስ ቃሉ እንደሚለው የእግዚአብሔር “ቅዱሱ” መበስበስን አያይም (መዝሙር 16፡10)፣ እናም ኢየሱስ ፈጽሞ መበስበስን አላየም፣ ከሞተ በኋላ እንኳ (ሐዋ. 13፡32-37 ተመልከት)። በክርስቶስ ትንሣኤ ላይ ተመሥርቶ ነው ጳውሎስ የሰበከው፣ “እንግዲህ ወንድሞች ሆይ፥ በእርሱ በኩል የኃጢአት ስርየት እንዲነገርላችሁ፥ በሙሴም ሕግ ትጸድቁበት ዘንድ ከማይቻላችሁ ሁሉ ያመነ ሁሉ በእርሱ እንዲጸድቅ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን” (ሐዋ. 13፡38-39)።

የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የመለኮትነቱ የላቀ ማረጋገጫ ብቻ አይደለም፤ እሱ ደግሞ የብሉይ ኪዳን ትንቢቶች፣ እነርሱም ስለ ኢየሱስ መከራና ትንሣኤ የተተነበዩትን ማረጋገጫ የሚሆን ነው (ሐዋ. 17፡2-3 ተመልከት)። የክርስቶስ ትንሣኤ ደግሞ የራሱን ቃል ያረጋግጣል፣ በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ የተናገረውን (ማርቆስ 8:31፤ 9:31፤ 10:34)። ኢየሱስ ክርስቶስ ካልተነሣ፣ እንግዲያውስ እኛ ምንም ተስፋ አይኖረንም፣ ለመነሣታችን። በርግጥ፣ ከክርስቶስ ትንሣኤ በቀር፣ አዳኝ አይኖረንም፣ ድኅነት አይኖረንም፣ ብሎም የዘላለም ሕይወት ተስፋ አይኖረንም። ጳውሎስ እንዳለው፣ እምነታችን “ከንቱ” ይሆናል፣ ወንጌልም ተያይዞ ሥልጣን-የለሽ ይሆናል፣ ኃጢአታችንም ይቅር ሳይባል ይቀራል (1 ቆሮንቶስ 15፡14-19)።

ኢየሱስ ብሏል፣ “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ” (ዮሐንስ 11፡25)፣ እናም በዛ መግለጫ የሁለቱም ምንጭ መሆኑን አስረግጧል። ከክርስቶስ ውጭ ትንሣኤ አይኖርም፣ የዘላለም ሕይወት አይኖርም። ኢየሱስ ሕይወትን ከመስጠት በላይ አድርጓል፤ እሱ ሕይወት ነው፣ በዚህን ምክንያት ነው ሞት በእርሱ ላይ ሥልጣን የሌለው። ኢየሱስ ሕይወቱን በመተማመኛ ሰጥቷል፣ በእርሱ በሚያምኑት ላይ፣ እናም እኛ በሞት ላይ ድል ማድረግን መካፈል እንድንችል (1 ዮሐንስ 5:11–12)። በኢየሱስ ክርስቶስ የምናምን በግላችን ትንሣኤን እናገኛለን፣ ምክንያቱም ኢየሱስ የሰጠን ሕይወት ስላለ፣ ሞትን ድል ነሥተናል። ሞት ያሸንፍ ዘንድ አይችልም (1 ቆሮንቶስ 15:53–57)።

ኢየሱስ “ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል” (1 ቆሮንቶስ 15፡20)። በሌላ አገላለጽ፣ ኢየሱስ ከሞት በኋላ ያለውን የሕይወት መንገድ መርቷል። የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ለሰው ልጆች ትንሣኤ ምስክር ይሆን ዘንድ ጠቃሚ ነው፣ እሱም የክርስቲያን እምነት መሠረታዊ ዶክትሪን ነው። ከሌሎቹ ሃይማኖቶች በተለየ፣ ክርስትና ከሞት በላይ የሆነ መሥራች አለው/ወርሷል፣ እሱም ተከታዮቹ ተመሳሳይ እንደሚያደርጉ ተስፋ የሰጠ። ሌሎች ሃይማኖቶች በሰዎች ወይም በነቢያት ነው የተመሠረቱት፣ መጨረሻቸውም መቃብር የሆነ። እንደ ክርስቲያኖች፣ አምላክ ሰው እንደ ሆነ እናውቃለን፣ ስለ ኃጢአታችን ሞቷል፣ በሦስተኛው ቀን ተነሥቷል። መቃብር ሊይዘው አይችልም። እሱ ሕያው ነው፣ እናም ዛሬ በመንግሥተ ሰማይ በአብ ቀኝ ተቀምጧል (ዕብራውያን 10፡12)።

የእግዚአብሔር ቃል ለአማኞች ትንሣኤ ዋስትና ይሰጣል፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ምጽአት ላይ፣ በቤተ-ክርስቲያኑ መነጠቅ ጊዜ። ይሄን መሰሉ ዋስትና ታላቁን የድል መዝሙር ያስገኛል፣ ጳውሎስ በ1 ቆሮንቶስ 15፡55 ላይ እንደጻፈው፣ “ሞት ሆይ ድል መንሣትህ የታለ? ሞት ሆይ መውጊያህ የታለ?” (ሆሴዕ 13፡14)።

የክርስቶስ ትንሣኤ ጠቀሜታ አሁን ለጌታ በምንሰጠው አገልግሎት ላይ ተጽዕኖ አለው። ጳውሎስ በትንሣኤ ላይ ያለውን ገለጻ በእነዚህ ቃላት ይደመድማል፡ “ስለዚህ፥ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ድካማችሁ በጌታ ከንቱ እንዳይሆን አውቃችኋልና የምትደላደሉ፥ የማትነቃነቁም፥ የጌታም ሥራ ሁልጊዜ የሚበዛላችሁ ሁኑ” (1 ቆሮንቶስ 15፡58)። በአዲስ ሕይወት እንደምንነሣ በማወቃችን ምክንያት፣ ስደትንና አደጋን ስለ ክርስቶስ ብለን መታገሥ እንችላለን (ቁጥር 30-32)፣ ጌታችን እንዳደረገው ሁሉ። በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ምክንያት፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ክርስቲያን ሰማዕታት፣ በታሪክ ላይ፣ በፍቃዳቸው ምድራዊ ሕይወታቸውን ለውጠዋል፣ ለዘላለም ሕይወት እና ለትንሣኤ ተስፋ።

ትንሣኤ ለእያንዳንዱ አማኝ ስኬታማነትና ክብራዊ ድል ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቷል፣ ተቀብሯል፣ እናም በሦስተኛው ቀን ተነሥቷል፣ መጽሐፍ እንደሚል (1 ቆሮንቶስ 15፡3-4)። እናም ተመልሶ ይመጣል! በክርስቶስ የሞቱት ይነሣሉ፣ እናም በምጽአቱ ጊዜ በሕይወት ያሉ ተለውጠው፣ አዲስ፣ የከበረ አካል ይቀበላሉ (1 ተሰሎንቄ 4፡13-18)። የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ለምን ጠቃሚ ይሆናል? እሱ ኢየሱስ ማን እንደሆነ ያረጋግጣል። እሱም ኢየሱስ በእኛ ምትክ የከፈለውን መሥዋዕትነት እግዚአብሔር እንደተቀበለው ያሳያል። እሱም እግዚአብሔር እኛን ከሞት እንደሚያስነሣን ሥልጣን እንዳለው ያሳያል። እሱም በክርስቶስ የሚያምኑ አካላት እንደ ሞቱ እንደማይቀሩ ይልቁንም ለዘላለም ሕይወት እንደሚነሡ ዋስትና ይሰጣል።

English



ወደ አማርኛ መነሻ ገጽ ለመመለስ

የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ጥቅሙ ምንድነው?
© Copyright Got Questions Ministries