settings icon
share icon
ጥያቄ፤

ክርስቲያን ደኅንነቱን ሊያጣ ይችላልን?

መልስ፤


በቅድሚያ ክርስቲያን የሚለው ቃል መብራራት አለበት። “ክርስቲያን” ጸሎትን የሚያደርስ ሰው አይደለም፣ ወይም በቤተ ክርስቲያን ደጃፍ የሚመላለስ፣ ወይም በክርስቲያን ቤተሰብ ያደገ። እነዚህ እያንዳንዱ ነገሮች የክርስቲያን ልምምዶች ሊሆኑ ቢችሉም፣ ክርስቲያን የሚያደርጉ አይደሉም። ክርስቲያን ማለት ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ ብቸኛ አዳኝ አድርጎ ሙሉ ለሙሉ ያመነ ሰው ማለት ነው፣ እና ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ ያድርበታል (ዮሐንስ 3:16፤ ሐዋ. 16:31፤ ኤፌሶን 2:8–9)።

ስለዚህ፣ ይሄንን ፍቺ ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ክርስቲያን ደኅንነትን ሊያጣ ይችላልን? እሱም ዋነኛ ጠቃሚ ጥያቄ ነው። እሱን ለመመለስ የተሻለው መንገድ ሊሆን የሚችለው፣ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ደኅንነት ምን እንደሚል መመርመርና ደኅንነትን ማጣት ምን ማለት እንደሆነ በተገቢው በመመርመር ነው፡

ክርስቲያን አዲስ ፍጥረት ነው። “ስለዚህ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ ሁሉም አዲስ ሆኖአል” (2 ቆሮንቶስ 5፡17)። ክርስቲያን እንዲያው “የተሻሻለ” ሰው ቅጂ አይደለም፤ ክርስቲያን ባጠቃላይ አዲስ ፍጥረት ነው። እሱ “በክርስቶስ” ነው። ክርስቲያን ደኅንነቱን እንዲያጣ፣ አዲሱ ፍጥረት መጥፋት አለበት።

ክርስቲያን የተዋጀ ነው። “ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከከንቱ ኑሮአችሁ በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ (1 ጴጥሮስ 1:18–19)። የተዋጀ የሚለው ቃል የሚያመለክተው ግዢ ለመፈጸም፣ ዋጋ ይከፈላል ለማለት ነው። እኛ የተገዛነው በክርስቶስ ሞት ዋጋ ነው። ክርስቲያን ደኅንነቱን እንዲያጣ፣ እግዚአብሔር ራሱ ግዢውን መሰረዝ ይኖርበታል፣ የከበረውን የክርስቶስን ደም የከፈለበትን ግለሰብ።

ክርስቲያን የጸደቀ ነው። “እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፤ (ሮሜ 5፡1)። መጽደቅ ማለት ጻድቅ እንደሆነ ማወጅ ነው። ኢየሱስን እንደ አዳኛቸው አድርገው የተቀበሉት ሁሉ በእግዚአብሔር “ጻድቅ እንደሆኑ ታውጆላቸዋል።” ክርስቲያን ደኅንነቱን እንዲያጣ፣ እግዚአብሔር ወደ ቃሉ ወደ ኋላ ተመልሶ “አለ ማወጅ” አለበት፣ ቀደም ሲል ያወጀውን። ከኃጢአት ነጻ የወጡት እንደገና ተፈትሸው ኃጠአተኝነታቸው መታወቅ አለበት። እግዚአብሔር ውሳኔውን መገልበጥ ይኖርበታል፣ ከመለኮታዊ መንበሩ የሰጠውን።

ክርስቲያን የዘላለም ሕይወት ተስፋ ያለው ነው። “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና” (ዮሐንስ 3፡16)። የዘላለም ሕይወት ማለት በመንግሥተ ሰማያት ከእግዚአብሔር ጋር ለዘላለም ለመኖር ያለ ተስፋ ነው። እግዚአብሔር ቃል ገብቷል፣ “እመኑ የዘላለም ሕይወትም ይኖራችኋል።” ክርስቲያን ደኅንነቱን እንዲያጣ፣ የዘላለም ሕይወት ፍቺ ዳግም መብራራት አለበት። ክርስቲያን ለዘላለም እንዲኖር ቃል የተገባለት ነው። ዘላለማዊ ማለት “ለዘላለም” ማለት አይደለምን?

ክርስቲያን በእግዚአብሔር ምልክት የተደረገበትና በመንፈስ ማኅተም የተደረገበት ነው። “እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፥ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤ እርሱም የርስታችን መያዣ ነው፥ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ፥ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል” (ኤፌሶን 1፡13-14)። ባመነበት ቅጽበት፣ አዲሱ ክርስቲያን ምልክት ይደረግበታል፣ ብሎም በመንፈስ ይታተማል፣ እሱም በተስፋው ቃል የሰማያዊ ርስታችን መያዣ ዋስትና ነው። የመጨረሻው ውጤት የእግዚአብሔር ክብር መመስገን ነው። ክርስቲያን ደኅንነቱን እንዲያጣ እግዚአብሔር ምልክቱን ማጥፋት አለበት፣ መንፈሱን መውሰድ ይኖርበታል፣ ክፍያውን ይሰርዛል፣ የተስፋ ቃሉን ይሰብራል፣ ዋስትናውን ይሰርዛል፣ ርስቱን ይጠብቃል፣ ምስጋናውን ያግዳል፣ ክብሩን ያላላል።

ክርስቲያን የክብር ዋስትና ያለው ነው። “አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው” (ሮሜ 8፡30)። እንደ ሮሜ 5፡1፣ ጽድቅ የእኛ ነው፣ በእምነት ቅጽበት ላይ። እንደ ሮሜ 8፡30፣ መክበር የሚመጣው በጽድቅ ነው። እግዚአብሔር ያጸደቃቸውን ሁሉ እንዲከብሩ የተስፋ ቃል ሰጥቷል። ይህም የተስፋ ቃል የሚፈጸመው ክርስቲያኖች ፍጹም የሆነውን የትንሣኤ አካል በመንግሥተ ሰማይ ሲቀበሉ ነው። ክርስቲያን ደኅንነቱን የሚያጣ ከሆነ፣ እንግዲያውስ ሮሜ 8፡30 ስህተት ነው ማለት ነው፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር የመክበርን ዋስትና ቀድሞ ለወሰናቸው፣ ለጠራቸው፣ እና ላጸደቃቸው ሁሉ መስጠት ስለማይችል።

ክርስቲያን ደኅንነትን ሊያጣ አይችልም። አብዛኛው፣ ሁሉም ባይሆን፣ መጽሐፍ ቅዱስ ክርስቶስን በተቀበልንበት ጊዜ፣ በእኛ ላይ ይፈጸማል ያለው፣ ዋጋ ቢስ ይሆናል፣ ደኅንነት የሚጠፋ ከሆነ። ደኅንነት የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፣ እናም የእግዚአብሔር ስጦታዎች “አይሰረዙም” (ሮሜ 11፡29)። ክርስቲያን አዲስ የተወለደ ላይሆን አይችልም። የተዋጀ ያልተገዛ/ዋጋ ያልተከፈለበት ሊሆን አይችልም። የዘላለም ሕይወት ጊዜያዊ ሊሆን አይችልም። እግዚአብሔር የገባውን ቃል አለመፈጸም አይችልም። ቅዱስ ቃሉ እንደሚለው እግዚአብሔር ሊዋሽ አይችልም (ቲቶ 1፡2)።

ክርስቲያን ደኅንነትን ሊያጣ አይችልም በሚለው እምነት ላይ ሁለት የተለመዱ ተቃውሞዎች፣ እነዚህን ልምዳዊ ጉዳዮች ግምት ውስጥ አስገቡ፡ 1) በኃጢአት በተሞላ፣ ንስሐ ባልገባ የሕይወት ስልት የሚኖሩት ክርስቲያኖች እንዴት ሊሆኑ ነው? 2/ እምነታቸውን የተዉትን እና ክርስቶስን የካዱት ክርስቲያኖች እንዴት ሊሆኑ ነው? የእነዚህ ተቃውሞዎች ችግር፣ እያንዳንዱ ራሱን “ክርስቲያን” ብሎ የሚጠራውን፣ ዳግም እንደ ተወለደ አድርጎ የመውሰድ ግምት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያውጀው እውነተኛ ክርስቲያን ቀጣይነት ባለው ንስሐ ባልገባበት ኃጢአት ውስጥ አይኖርም (1 ዮሐንስ 2:19)። እሱ ሃይማኖታዊ ሊሆን ይችላል፣ እሱም ከእይታ አኳያ መልካም ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን በእግዚአብሔር ኃይል ፈጽሞ ዳግም አልተወለደም። “ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ። ከእሾህ ወይን ከኩርንችትስ በለስ ይለቀማልን?” (ማቴዎስ 7፡16)። በእግዚአብሔር የተዋጀ የሚገባው፣ “…ለእግዚአብሔር ፍሬ እንድናፈራ፥ እናንተ ለሌላው፥ ከሙታን ለተነሣው፥ ለእርሱ ትሆኑ ዘንድ” (ሮሜ 7፡4)።

የእግዚአብሔርን ልጅ ምንም ነገር ከአብ ፍቅር አይነጥለውም (ሮሜ 8፡38-39)። ምንም ነገር ክርስቲያንን ከእግዚአብሔር እጅ አይነጥቀውም (ዮሐንስ 10:28–29)። እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ያስከብራል፣ የሰጠንንም ደኅንነት ያጸናል። መልካሙ እረኛ የጠፉትን በጎች ይፈልጋል፣ እናም፣ “ባገኘውም ጊዜ ደስ ብሎት በጫንቃው ይሸከመዋል፤ ወደ ቤትም በመጣ ጊዜ…” (ሉቃስ 15፡5-6)። በጉ ተገኝቷል፣ እናም እረኛው ሸክሙን በደስታ ይሸከመዋል፤ ጌታችን ሙሉ ኃላፊነቱን ይወስዳል፣ የጠፋውን በሰላም ወደ ቤት ያመጣ ዘንድ።

ይሁዳ 24-25 በተጨማሪ አጽንዖት ይሰጣል፣ ለአዳኛችን መልካምነትና ታማኝነት፡ “ሳትሰናከሉም እንዲጠብቃችሁ፥ በክብሩም ፊት በደስታ ነውር የሌላችሁ አድርጎ እንዲያቆማችሁ ለሚችለው ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም እስከ ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን።”

English



ወደ አማርኛ መነሻ ገጽ ለመመለስ

ክርስቲያን ደኅንነቱን ሊያጣ ይችላልን?
© Copyright Got Questions Ministries